በአንድ መጽናት አቃተኝ

የአንባቢ ጥያቄ፦ የዕድል ነገር ሆኖ አብዛኛውን ጊዜ የምፈልጋቸውን ሴቶች አገኛለሁ። ነገር ግን አንዴ ተዋውቄ ከበዳኋቸው በኋላ ጠንካራ ግንኙነት መመስረት አልችልም። እንደገና ሌላ ፍለጋ እሄዳለሁ። ችግሬ ምንድነው?

የኛ ምላሽ፦ የችግርህ መንስዔ ሊሆኑ ይችላሉ ያልናቸውን ምክንያቶች እንደሚከተለው ዘርዝረናል፦

1) በአንድ ሴት ፀንቶ መገኘት ያስፈራህ ይሆናል።

2) ያየኻት ሴት ሁሉ ታምርኻለች።

3) ሴቶችን እንደ ካልሲ መቀያየር ያኮራኻል ወይም ያስደስትኻል። ያላቅምህ የምትንጠራራ፣ ጉረኛ ነህ።

4) ከመጠን በላይ ራስህን ትወዳለህ (ናርሲሲት ነህ)።

5) የምትገናኛቸውን ሴቶች በባሕሪ፣ በገንዘብ፣ በትምህርት ደረጃ ወይም በሌሎች መለኪያዎች አትመጥናቸውም ወይም አይመጥኑህም።

6) ሴትን የምትፈልጋት ለስሜት ማስታገሻነት ብቻ ነው።

7) ከአንዳቸውም ሴቶች ፍቅር ይዞህ አያውቅም።

8)ፍቅር ይዞህ ከነበረም፣ ያፈቀርካት ልጅ ስላላፈቀረችህ ወይም ትታህ ሌላ ወንድ ስለያዘች፣ ለሷ ያለህ ስሜት ገና አልበረደልህም። ስለዚህ እሷን ለመርሳት ወይም ለመበቀል ካገኘኻት ሴት ጋር ትወጣለህ።

9) ዘላቂ የፍቅር ጓደኛ ወይም ትዳር የምትፈልግበት ዕድሜ ላይ አይደለህም።

10) በሁሉም ነገር የምትስማማህን ሴት ስታገኝ እንዴት አድርገህ መያዝ እንዳለብህ አታውቅም።

ወ.ዘ.ተ.

ከነዚህ 10 ምክንያቶች ውስጥ ቢያንስ አንዱ አንተን የሚገልጽህ ከሆነ፣ ያን ባሕሪህን ወይም አቋምህን ልትለውጠው ወይም ልታሻሽለው ይገባል። ዘላቂ የሆነ ግንኙነት ዝም ብለህ በቀላሉ የምትጀምረውና የምትጨርሰው ነገር አይደለም። ፍሬያማ ግንኙነት ለመመስረት ጊዜህንና ጉልበትህን ማፍሰስ አለብህ። ጥሩ አፍቃሪና ታማኝ ሆኖ መገኘትም የግድ ነው። ግንኙነትን ግንኙነት የሚያደርገው ወሲብ ብቻ አይደለም። ፍቅር መኖር አለበት። የፋይናንስ አቅምም ወሳኝነት አለው።

“ከግንኙነት የምፈልገው ምንድነው?” ብለህ ራስህንም ጠይቅ። “ወሲብ ብቻ ነው ወይስ ከወሲብ በላይ የምፈልገው ነገር አለ? የምፈልገውን ነገር ማግኘት እችላለሁ? መስጠትስ እችላለሁ?” ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ካገኘህ፣ ስኬታማ ግንኙነት መመስረት ትችላለህ።

3 thoughts on “በአንድ መጽናት አቃተኝ

  1. እውነቱ ነው!! እንዲህ ዓይነት ሠው ከላይ የተጠቀሱት ባህሪ ያለው ነው፡፡ እደፈዋለህ!!!!
    ወልዱ ነኝ

Leave a comment